የሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት አሜሪካ በጃፓን ላይ ሁለት አውቶሚክ ቦንብ ጣለች፡፡ በርካታ ሕዝቦች ከመቅጽበት እቺን አለም ተሰናበቱ፡፡ በጊዜው የጃፓን መሪ ሐገራቸው ላይ ጥቃት እንደተሰነዘረ ዜናው ደረሳቸው፡፡ ሁኔታው ታላቅ መርዶ ነበር ፡፡ ቅድሚያ የጠየቁት ነገር አንድ ነው “ምን ያህል መምህራን የሚተርፉ ይመስላችኋል?” ፡፡
በርግጥ በእንዲህ አይነት ጅምላ ጨራሽ ጥቃት ውስጥ መምህርን መርጦ የሚተው ተአምር የለም፡ ይኽ ይጠፋቸዋል ብለን አንገምትም፡፡ ሆኖም ስለሔደው ከማሰብ በላይ ስለሚመጣው ማሰብ የባለተስፋዎች አለም መሆኑን ቢረዱ እንጂ፡፡ ግን ለምን መምህር? ታላላቅ ባለህልሞች እና ሳይንቲስቶች፣ ቀመር ፈጣሪች እና ተአምር ሰሪዎች ባሉባት ሀገር እኒህን ሰው መምህር እንደምን እራባቸው?
እንዲህ መስለኛል፤ ጃፓንን እዚህ ግቢ ከማትባልበት ሥፍራ አንስቶ ኃያል እና ታላቅ ያደረጋት እውቀት ፈላጊነት እንጂ እውቀት እራሱ አደለም፡፡ ይሔንን ደግሞ የሰጣት መምህራኗ ናቸው፡፡ እውቀት ለአንድ ውስን ነገር መፍትሔ ይሆናል፡፡ እውቀት ፈላጊነት ግን በማይቋረጥ ሂደት ውስጥ ችግሮችን እየፈቱ ምስጢሮችን ገሀድ እያወጡ መኖር ነው፡፡ በሌላ አባባል አንድ ኢንጂነር ህንጻ ሰርቶ የመኖሪያ ችግርን ያቃልላል ለነዋሪው አኗኗሩን ግን ሊያሳየው አይቻለውም፡፡ አንድ ዶክተር በሽታን ያክማል እንጂ ጤናን አይጠብቅም፡፡ በፎቅ የመኖርን ስርአትም ሆነ ጤናውን ተከታትሎ የመጠበቅ ልማድ የእያንዳንዱ ሰው ፈንታ ነው፡፡ ደግሞም ሁለቱም የዛሬን ችግርን ቢያቃልሉ እንጂ ለነገው ችግር መፍትሔ አይሆኑም፡፡ ይሄን እውቀት ፈላጊነትን ሊሰጥ የሚችለው መምህር ብቻ ነው፤ መምህር ባለበት እውቀት መፈለግ ብርቱ ትሆናለች፡፡
እውቀትን መፈለግ ስትሰፋ ድንቁርና፣ ለኔ ይድላኝ ማለት እና ከኔ በላይ ማን አለብኝነት ስፍራ አይኖራቸውም፡፡ ህንጻዎችን በጥቂት ጊዜያት ውስጥ ሊገነቡና ከተማ በተንቆጠቆጡ የድንጋይ ጫካ ሊሞሉ ይችላሉ፡፡ እነዚህ ህንጻዎችን የኔ የሚላቸውና የእውቀት ፍሬ መሆናቸውን የሚረዳ የለማ ባለ አዕምሮ ህዝብ ከሌለን ግን እንደ ሔሮሽማ እና ናጋሳኪ ለመውደማቸው ከተሰሩበት ጊዜ እጅግ ያነሰ ሰአታት ብቻ ነው የሚወስደው፡፡
ዋናው ጭብጣችን እውቀትን መፈለግ ነው፡፡ ጃፓን ከዛ ሁሉ መአት ተርፋ አሁንም ታላቅ ሆና እንድትታይ ያደረጋት ምስጢር ይኽው እውቀትን ፍጊነቷ ነው፡፡ አንድ ህዝብ እውቀትን መፈለግ በመምህሩ ይማራል፡፡ ከትምህርት ቤት ከወጣ በኋላም ግን መምህሩ በሰጠው ዋና መሳሪያ አማካይነት እውቀትን ሲያስስ ይኖራል፡፡ ይህ መሳሪያ ደግሞ ንባብ ነው፡፡ ከንባብ ውጪ ሆነ ህዝብ ደካማ ነው፡፡ በተለይ በዚህ መረጃ ኃይል በሆነበት በዘመነ-ልዑላዊነት ውስጥ የማያነብ ህዝብ ያላት ሀገር የመጥፊያዋን ጉድጓድ እየቆፈረች ነው ማለት ይቀላል፡፡
እውቀትን የማያስስ ንባብን የሚጠላ ባለስልጣን የከበባት ሀገር መከራዋ ረዥም ነው፡፡ ዛሬ ያለንበትን ችግር ሁሉ መልስ ሚሰጡ በርካታ አቋራጮችን ልናገኝ እንችላለን፡፡ ድልድዮችን ህንጻዎችን እርሻዎችን መንዶችን የሚሰራ ድርጅት ከፍለን ከውጭ እናስመጣው ይሆናል፡፡ የተሰሩትን ስራዎች ምንገለገልባቸው ግን እኛው ነን፡፡ ደግሞም ለዛሬ ችግራችን መፍትሔ ሊሆኑ እንጂ ለነገው ችግራችን ዋስትና መሆን አይችሉም፡፡ ስለዚህም እውቀት አሳሽ፣ ንባብ ወዳድ ህዝብ ያስፈልገናል፡፡
ይቀጥላል