2013 ኦገስት 29, ሐሙስ



የሚስኪኖች አመጽ
ሀገር ምድሩ ሁሉ ተሸጦ በገንዘብ
የኛን ስፍራ ማጣት ህዝብ እንዴት ይገንዘብ፡፡
አላይ ላለ አይን ለማይሰማ ጆሮ
አመጽ አንስተናል ከዛሬ ጀምሮ
ካጣን ትንሽ ስፍራ ለመላወሻ እንኳን
ለሚሻግት እህል ማስጫ ከተቸገርን
ምንዱባን ተነሱ አብዮት አቃጥሉ
የደሀ ንብረት ነው የሐብታም ግዛት ሁሉ፡፡
ሰኔ 26/2005

2013 ጁላይ 24, ረቡዕ

የይታገሱ መስኮት: ስለራስ የሳሉትን ምስል ማምለክ እና ራስ የሳሉትን ስዕል መፍራት

የይታገሱ መስኮት: ስለራስ የሳሉትን ምስል ማምለክ እና ራስ የሳሉትን ስዕል መፍራት

ስለራስ የሳሉትን ምስል ማምለክ እና ራስ የሳሉትን ስዕል መፍራት



ሁለት አደገኛ ነገሮችን አውቃለሁ፤ ስለራስ የሳሉትን ምስል ማምለክ እና ራስ የሳሉትን ስዕል መፍራት፡፡ ሁሌ ባየኋት ቁጥር የምትገርመኝ ስዕል አለች፡፡ ስዕሏ መስታወት ፊት የቆመች ድመትን ይዟል፡፡ በመስታወቱ ውስጥ ያለው ምስል ግን የድመቷ ሳይሆን የአንበሳ ነው፡፡ አንዳንዴ አካባቢያችንን ስናስተውል ከሆኑት በላይ ለራሳቸው ስዕል ታላቅነትን የሰጡ ለዛም የተሳሳተ ምስል የሚንበረከኩ በርካቶች ናቸው ፡፡ በፖለቲካውም፣ በመንደሩም፣ በመስሪያ ቤቱም ሆነ በጓደኝነቱ እነዚህን ማግኘት አይከብድም፡፡ እነዚህ ሰዎች “እኔ” ከሚል ቃል የበለጠ የሚያውቁት የሌለ ይመስላሉ፡፡ የሁሉም ነገር ባለቤት እና ፈጣሪ አድርገው ራሳቸውን ያስባሉ፡፡ ሲመስላቸው እነሱ ከመምጣታቸው አስቀድሞ ምድር እንኳን ምህዋሯን ጠብቃ እንዴት ልትዞር እንደቻለች ይገርማቸዋል፡፡ ያንንም መስማት እሱንም መናገር አይሆንላቸውም፡፡ ሊያወሩም ሆነ ሊናገሩ የሚፈልጉት እነሱ ስላበረከቱት አስቷጽዖ እንጂ ስለሌሎች አበርክቶ አይደለም፡፡
ብዙም ርቀን አንሂድ፤ በቀኝም ሆነ በግራ የተሰለፉትን ፖለቲከኞቻችንን ማየት በቂ ነው፡፡ የነገሮች ሁሉ ቁልፍ የሆኑ መሆኑን ሊነግሩን እና ሊመክሩን ይነሳሉ፡፡ እነሱ ጋ ፈጽሞ መሳሳት ይሉት ታሪክ የሌለ ያስመስሉታል፡፡ የመፍትሄዎች ሁሉ መፍትሄ ከነርሱ ውጪ እንደሌለ ይነግሩናል፡፡ ለመናገር እንጂ ለመስማት ጆሮ የተፈጠረባቸው አይመስሉም፡፡ ስለራሳቸው የሳሉት ስዕልን ተጠራጥረው አያውቁም፡፡ በነሱ መፍትሔ ሐገር የረጋ ህዝብ የተጋ ይመስላቸዋል፡፡ የሚለኩት እና የሚመትሩት እነሱ ካሉበት አቅጣጫ ብቻ ስለሆነ ልዩነቱን መረዳት አይቻላቸውም፡፡ ምናልባት የቆሙበት አላማ የተሳሳተ ሊሆን እነደሚችል ፈጽሞ ማሰብ አይሹም፡፡ ከእውነታው ጋር ሲፋጠጡ ማጥፊያ እንጂ መታጠፊያ መንገድ የላቸውም፡፡
ይህ አይነት ስለራሳችን የተጋነነ ስዕል መስጠት ከአደገኛ በላይ አደገኛ ነው፤ የሰናዖር ውድቀትን ያመጣል፡፡ አለአግባብና አለአቅም አየር ላይ መንሳፈፍ ከእውነተኛው ማንነት ጋር መፋጠጥ ሲመጣ ማረፊያ ያሳጣል፡፡ በራስ መተማመን ደግ ነገር ነው፤ በራስ ማመን (ራስን ማምለክ) ግን ዋጋ ያስከፍላል፡፡ አንዳንዶች እጃቸው ላይ ያለው ነገር አስተማማኝ እና የማይናድ ይመስላቸዋል፡፡ እውቀት ማለት ያልታወቀ ነገር እንዳለ ማወቅ ጭምር ነው፡፡ ስለዚህ ሁሉንም መጠርጠሩ ይበጃል፡፡ የዛሬው ማወቃችን ነገ አላዋቂነት እና የተሳሳተ ሊባል እደሚችል ማመን ተገቢነት ይኖረዋል፡፡ ማመንም ልክ ያስፈልገዋል ከእኔ ርዕዮተ አለም ውጪ ላሳር፣ ከኔ ሃይማኖት ውጪ ዉጉዝ፣ ከኔ ዕውቀት ውጪ ድንቁርና ማለት ራስን ማምለክ ነው፡፡ ትንሽም ቢሆን አቋማችንን መጠራጠር የእድገት እና የእውነት በር ነው፡፡
ሁለተኛው አደገኛ ነገር የራስን ምስል መፍራት ነው፡፡ ይሄኛው ደግሞ በጣም የከረረ ጥርጣሬና ፍርሐት ነው፡፡ ሰሞኑን አንድ ወዳጄ ያጫወተኝን አንድ ታሪክን ላስቀድም፡፡ በአንድ መንፈሳዊነት በበረታበት ገዳም ውስጥ የነበሩ መነኩሴ ሰይጣን ሁልጊዜ ከጸሎት ሊያስታጉላቸው እንደሚታገል ያምናሉ፡፡ እያንዳንዷም ቀን እንዳትባክን በመጠንቀቅ በማነጋጊያው ላይ ለሚጸለየው ጸሎት ማልደው ጨለማው ሳይወግግ ወደቤተክርስቲያን ያቀኑ ነበር፡፡ አንድ ቀን ቀድመው ተነስተው ከለሊቱ በአስር ሰዓት ወደ ቤተክርስቲያን ያመራሉ፡፡ በበአታቸው እና በቤተክርስቲያኑ መካከል አንዲት ጠባብ ድልድይ አለች፡፡ እዚች ድልድይ ጋ ሲደርሱ ከድልድዩ አቅጣጫ አንድ ጠቆር ያለ ነገር ሲንቀሳቀስ ተመለከቱ፡፡ አባ አማተቡ፤ ያ ነገር ግን አልጠፋም ባለበት ረጋ፡፡ አባ መቁጠሪያቸውን አውጥተው ባሉበት ቆመው ጸሎታቸውን ጀመሩ፡፡ ያሰቡት ሰይጣን ግን ከቦታው አይንቀሳቀስም፡፡ እሱም የድልድዩ መጨረሻ ላይ እንደቆመ ነው፡፡ አባ ውጊያቸውን በማፋፋም መከላከላቸውን አጠናከሩ፡፡ ከማለዳው ጸሎት ያስቀራቸውን ሰይጣን በትጋት ባሉበት ቦታ ቆመው ሳይሸሹ ተዋጉት፡፡ አባ በቆሙበት ጨለማው እየለቀቀ የማለዳውም ጸሎት እያለቀ መጣ፡፡ በብርሐኑ አተኩረው ሲያስተውሉ እሱም እንደሳቸው ከፊቱ የቆመውን ሰይጣን በጸሎት እየታገለ ያለውን የገዳሙን መነኩሴ ተመለከቱ፡፡    
ከመጠን ያለፈ ተጠራጣሪነት ከመዳረሻችን ያዘገየን ወይም ያስቀረን በርካቶች ነን፡፡ ሁሉንም እኔን ለመበደል የተደረገ እኔን ለማዋረድ የተነገረ ነው የምንል ከሆነ አደገኛ ነው፡፡ ይህ ከመጠን በላይ የሆነ መጠራጠር ባልተረጋገጠና እራሳችን በሰራነው ስዕል እየታገዘ የበታችነት ስሜታችንን በማባባስ የቆቅ ኑሮ እንድንኖር ያደርገናል፡፡ እከሌ ይጠላኛል እከሌ ያጠቃኛል ብሎ ማሰብ ሰላም አይሰጥም፡፡ በተለይም ዉሱንነት ላለበት ሰው ራሱን ጠብቆና ደብቆ ላይኖር ነገር ህሌናን ይረብሻል፡፡ ይሔኛው ዘር ይንቀኛል ስለኔ እንዲህ ብሎ ያስባል የሚል የከረረ አመለካከት ደግሞ የባሰ ህዝብን ይበጠብጣል፡፡ በርግጥም እንዲህ ያለ የሐሳብ መረበሽ ያለባቸው ጥቂቶች አይደሉም፡፡ በስነ አምሮም ጥናትም ራሱን የቻለ በሽታ መሆኑ ታውቆ ህክምና ይሰጣል፡፡ ችግሩ ግን እነዚህ ሰዎች ህመም መሆኑን አያምኑም ፡፡ ጤነኛ መስለው በየቢሮው በኃላፊነት ተቀምጠዋል፡፡ በየመድረኩ ንግግር አዋቂ ተብለው ጥላቻን የሚሰብኩ ህዝብም የሚያዳምጣቸው ናቸው፡፡
እንደነዚ አይነት ራሳቸው የሳሉትን ምስል የሚፈሩ ተጠራጣሪዎች ሊደርሱበት የሚያልሙትን ነገር ከመያዝ ይልቅ በህሌናቸው ከሳሉት ስዕል ጋር ሲላፉ ዕድሚያቸውን ያሳልፋሉ፡፡ የበዛ ጥርጣሬ ሰላም የለውም፣ በአካባቢው ለሚገኙ ሌሎችም ሰላም አይሰጥም፡፡ እያንዳንዷን ቃል እየሰነተቁ እንዲህ ሊለኝ ፈልጎ ነው እያንዳንዷን የታሪክ ሰበዝ እየለቀሙ ዛሬም እንዲህ ሊያደርጉን አቅደው ነው ማለት እረፍት ያሳጣል፡፡ የዚህ አይነት ሰዎች ጥፋታቸው የትዬ ለሌ ነው፤ ፈሪ ሲደነብር ጀግናን ያስንቃል፡፡
ሐሳቤን ልጠቅልል ለራስ የሰጠነውን ስዕል በማምለክ እና ራስ የሳሉትን ምስል በመፍራት መካከል ያለው ልዩነት በከንቱ መወጠር እና አጉል መኮስመን ብቻ ነው፡፡ በተረፈ ሁለቱም የአንድ ሸማ ሁለት ጥለት መልክ ናቸው፤ የውድቀት ቁልቁለት፡፡  
   

2013 ሜይ 3, ዓርብ

ባለጸጋ ሰው

በምሬት ተሞልተው በአውድ ባደባባይ ሰዎች ይዘልፋሉ
በጓዳ ጎድጓዳ ሌቦች ተደራጅተው ደሀ ይዘርፋሉ
መግቢያ የጨነቀኝ መሸሸጊያ አጥቼ ቆሚያለሁ ካውላላ
ከተደበቀ እውነት ከሰዎች አሰሳ ከእልፍ ምላስ ኋላ
ማነው እኔን ያየ? መልኬን ያስተዋለ ነውሬን የገለጠ
ማነው ሀብቴን ያየ? ከተሸሸገ ሀብት የኔን የመረጠ
ኑልኝ ነጣቂዎች ደሃን አትምዝብሩ ከኔ አለ የላቀ
ዝቃችሁ ማትገፉት የተሸሸገ ሀብት ለአይን የረቀቀ
የያዝኩት በጽኑ ከሌሎች ጠብቄ ከነፍሴ እኩሌታ
አለላችሁ ሀብት አለላችሁ ገንዘብ ለጊዜ ያልተረታ
ሰብ የሚባል ሀውልት ሰው ይሉትን ቅርስ ያጣችሁት ከቶ
እኔ ዘንድ ተኝቷል እናንተ ውስጥ ሞቶ፡፡
ኑልኝ ዘላፊዎች ተጯጯኹ ደግሞ አዲስ ስም ሰይሙ
‘ሰው’ ከመባል ውጪ ለሰው እውነት የለም የሚከብር ስሙ
ስደቡት ይኽን እኔ ‘ሰው’ በሉት ደግማችሁ
ከሰው ተለይቷል ጋርዮሽ ላይ ቆሟል እናንት ሰልጥናችሁ፡፡
ዛሬም “እኛ” ይላል ብቻውን ካውላላ ቆሞ ተገትሮ
አይታችሁ አታውቁም እንዲህ ያል ደንቆሮ::
ተዉ አትድከሙ አይጥበብ ቴራሱ አትሙሉ አደባባይ
ስድቡን የሚጓጓ ስሙ የናፈቀው ቆሟል ካይናችሁ ላይ
ተዉ አትባክኑ ዝርፊያውን አቁሙ ደሀ አይርገማችሁ
ከሁሉ የከበረ ሀብታም ባለጸጋ ሰው እዚህ አለላቹ፡፡
                             26/11/2004

2013 ኤፕሪል 27, ቅዳሜ

ባለጸጋ ሰው



በምሬት ተሞልተው በአውድ ባደባባይ ሰዎች ይዘልፋሉ
በጓዳ ጎድጓዳ ሌቦች ተደራጅተው ደሀ ይዘርፋሉ
መግቢያ የጨነቀኝ መሸሸጊያ አጥቼ ቆሚያለሁ ካውላላ
ከተደበቀ እውነት ከሰዎች አሰሳ ከእልፍ ምላስ ኋላ
ማነው እኔን ያየ? መልኬን ያስተዋለ ነውሬን የገለጠ
ማነው ሀብቴን ያየ? ከተሸሸገ ሀብት የኔን የመረጠ
ኑልኝ ነጣቂዎች ደሃን አትምዝብሩ ከኔ አለ የላቀ
ዝቃችሁ ማትገፉት የተሸሸገ ሀብት ለአይን የረቀቀ
የያዝኩት በጽኑ ከሌሎች ጠብቄ ከነፍሴ እኩሌታ
አለላችሁ ሀብት አለላችሁ ገንዘብ ለጊዜ ያልተረታ
ሰብ የሚባል ሀውልት ሰው ይሉትን ቅርስ ያጣችሁት ከቶ
እኔ ዘንድ ተኝቷል እናንተ ውስጥ ሞቶ፡፡
ኑልኝ ዘላፊዎች ተጯጯኹ ደግሞ አዲስ ስም ሰይሙ
‘ሰው’ ከመባል ውጪ ለሰው እውነት የለም የሚከብር ስሙ
ስደቡት ይኽን እኔ ‘ሰው’ በሉት ደግማችሁ
ከሰው ተለይቷል ጋርዮሽ ላይ ቆሟል እናንት ሰልጥናችሁ፡፡
ዛሬም “እኛ” ይላል ብቻውን ካውላላ ቆሞ ተገትሮ
አይታችሁ አታውቁም እንዲህ ያል ደንቆሮ::
ተዉ አትድከሙ አይጥበብ ቴራሱ አትሙሉ አደባባይ
ስድቡን የሚጓጓ ስሙ የናፈቀው ቆሟል ካይናችሁ ላይ
ተዉ አትባክኑ ዝርፊያውን አቁሙ ደሀ አይርገማችሁ
ከሁሉ የከበረ ሀብታም ባለጸጋ ሰው እዚህ አለላቹ፡፡
                             26/11/2004

ኮከብ ነህ ርችት?

በዘመን የማትፈርስ በጊዜ ማትጠፋ
ጥበብ ሲሉኽ ማትጠብ ሲሉ እማትሰፋ
በህያው ሰማይ ላይ ጸንተህ የምትቆም
እኩል የሚገለጽ ብርሀንህ ላለም
ነህ ወይ ተወርዋሪ ነህ ወይ ያጥቢያ ኮከብ
የማታከራክር በሰማያት ክበብ
ንገረኝ በሞቴ ምንድነህ አነንተ ሰው
ላንድ ቀን ቢሆንም ቀኔን አታምሰው፡፡
ከሰሜን ከደቡብ ከምስራቅ ወይ ምራብ
ሊያይኽ ለሚፈልግ ማንህን ለሚራብ
እኩል ትታያለህ እንደኮከብ ሁሉ?
ወይስ መርጦ አቅጣጫ ይታያል ይበራል
                     የብርሀን ጸዳሉ?
በጊዜ በጩኽት በስሜት በረብሻ
በኮከብ ናፋቂ በሰዎች ጥቅሻ
ኮከብ እንድትመስል የተሰራኅ ብርሀን
ከቀናት በኋላ ጮራኅ ሚኮሰምን
ኮከብ ነኽ ወይ ሌላ አርቴፊሻል ነገር?
እውነትህን ግለጥ ሰው አታደናግር
ትሆን ወይ ርችት የበአል መድመቂያ
ከቀናት አንዱን ቀን በተለይ ማሞቂያ
ሰው እንደወደደው ቀለሙን ቀብቶ
በተኳሹ መሻት በተኳሹ ብልሐት 
                         ሽቅብ ከላይ ወጥቶ
ሲፈልግ ነጭ ኮከብ ሲፈልግ ዘንባባ
ሆኖ እንደሚታይ ወጥቶ እንደሚገባ
ትሆን ሆይ ሺህ ቀለም ግራጫ ቀይ ጥቁር
ሰማያዊ ደማቅ አረንጓዴ ነገር
ሐምራዊ  ብርቱካን ቢጫ ወርቀ ዘቦ
ሰው አፉን ከፈተ ማንህን ተርቦ
ምንድነህ ተጠየቅ ማነህ ማን እንበልህ
እዩኝ የምትለን ካናት በላይ ወተህ
በሆታ ጫጫታ የነገስክ ከሰማይ
አንተ ብርሓንማ ኮኮቦችን መሳይ
ፊናህን ለይልን ታሪክህ ይተርተር
ኮኮብ ነህ እርችት ያ ዶሴህ ይበጠር
በጊዜ ምጣድ ላይ በስለህ እስክትመጣ
ከኮኮብ ከርችት አይኖርህም ዕጣ
                        27/12/2004

ደጅ ያደረ ልብ



የልጅነት ህልሜ ጠይሞ መጥቆርሽን ባየው በመልክሽ
ነፍስ አውቄ በዕውን አይኔን ገልጬ ባይሽ
ከፍቅር በቀር ከውስጤ የሚወጣኝ ፍላቂ
አጣሁ በውስጤ ትርጉሙን የመውደዴን ድቃቂ
ከማህጸንሽ በቅዬ ካንቺነትሽ ስር ብገኝም
በስምሽ ስም ገዝቼ ባንቺነትሽ ብጠራም
ቡራኬሽ ባይኖር በላዬ የ“እደግ” ምርቃት ቱፍታሽ
ባትረግሚኝም ቅሉ መኖሬ በዕጆችሽ ጣት ስታሽ
ፍቅሬ ጎመዘዘኝ እናቴ “እማማ” ያልኩሽ አቃረኝ
መውደድሽ ሬት ማቀፍሽ የሾኽ ሆኖ ተሰማኝ::
“ሰው ቦታን ይቀድሳል ቦታ ደግሞ ሰውን ይቀድሳል”
ይሉ ብሒል ጠፋኝ እና አግኝቶ ማመስገንን
ጀረጀርኩ ደጅሽ ላድር ወለለት ባይኖረው ድምጼ
ከጆሮ ደርሶ ባይገባ የእዬዬ ቅላጼ
“እሹሩሩ” መባሉ ቀርቶብኝ በልጅ ወግ መባበሉ
መቅለጥ መቅበጤ ቆይቶ “ስመኽኝ ውጣ” መባሉ
በወጉ ድምጼ ተሰምቶ ከደፍሽ ወድቄ ባደርኩ
የኽው ስልሽ ብተሰሚኝ ባለመስማትሽ ባላዘንኩ::
እናትዬ!
መውደዴ ኪሳራ ብቻ ሲሆን ማፍቀሬ ግርጥጫ
በምን ልታገስ መኖርን በጉስምት በንቅፍት ቁንጥጫ?
አግማስሽ ሆኜ መፈሪያሽ ትምክህትሽ እንዲሆን በኔ
ቢያስብ ቢያልምም እራሴ በራሡ ለራስ ብያኔ
ሰነጋኝ ጣትሽ ጨፍልቆ ካንቺ የዘመድኩት ወንድሜ
ከእጄ ቢያጣ ጠብ-መንጃ ይዞ አሲዞኝ ጉሜ::
አድሬ ላይቀር መንቃቴ ሌላ ጨለማን ላልናፍቅ
መጀርጀሬን ባርኪልኝ ቤት መመለስን እስካውቅ
“ካገሩ የወጣ ከቤቱ ካገሩ ደግሞ እስኪመለስ
ቢጭኑት ሚስኪን አህያ ቢጋልቡትም ያው ፈረስ”
ብሎ መፍራቱ ቀርቶብኝ ለማላውቀው ደጅ ቅልማጤ
ለዚህ እንኳን እንትፍ በይልኝ ስደቴ እንዳይሆን ምጤ
ታዲያ ምን ላድርግሽ እናቴ? ሌማትሽ ለኔ ሲርቀኝ
እልፍኝሽ በኔ ላይ ተዘግቶ ገረድ ቤትሽ ሲተርፈኝ
ጤፍሽ ለእኔ ተከቶ በዋሪያት ምግብ ስትሸኚኝ
ልጅ መባሌ ተረስቶ ባዳ ስሆን በቤቴ
መውደዴ ዋጋ ሲያጣ መፈቀር ሲሆን ጥማቴ
ታዲያ ምን ልበልሽ እማማ ላባብልሽ እንዴት አድርጌ?
ልምምጥ አላስተማርሽኝ የጭራ መቁላትን ብላጌ
ተለማምጠሸ አታውቂምና ከደጅሽ ያደረን ሁሉ
እኔም ከቶ አላደርገውም ያንቺው ልጅ ነኝና ቅሉ
የማንነቴ ምዕላድ የምንነቴ ግላጬ
የማህጸንሽ ተቋዳሽ የመታወቂያ ጭላጬ
ነኝ እና ያንቺ ግልባጭ ከ‘ድልሽ እድል ምጣባ
ካመልሽ አመል የምቆርስ ሲወዱኝ የማላውቅ ገሪባ
ባለሽበት ላግኝሽ እናቴ ወንድሜ ወርዶ ከላይሽ
ልጆችሽ በኩብላይ ሳያልቁ ሳይሞት መጻኢ እድልሽ
ደህና ሁኚ እናት አለም ወይኔ ልጆቼ ያስብልሽ
ጡትሽን መጠው አፍልቀው በወተትሽ እንዲያጥቡሽ
ወትሮስ ሲጠቅሱት ያልገባው ቢቆነጥጡት ይረዳ?
ከሜዳ ጠፋ ቢሉ ከጫካ ይሸመት የል እዳ፡፡
4/12/93
ለሊት 8፡00
ቦሌ አይሮፕላን ማረፊያ

2013 ማርች 26, ማክሰኞ

እውቀትን መፈለግ

የሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት አሜሪካ በጃፓን ላይ ሁለት አውቶሚክ ቦንብ ጣለች፡፡ በርካታ ሕዝቦች ከመቅጽበት እቺን አለም ተሰናበቱ፡፡ በጊዜው የጃፓን መሪ ሐገራቸው ላይ ጥቃት እንደተሰነዘረ ዜናው ደረሳቸው፡፡ ሁኔታው ታላቅ መርዶ ነበር ፡፡ ቅድሚያ የጠየቁት ነገር አንድ ነው “ምን ያህል መምህራን የሚተርፉ ይመስላችኋል?” ፡፡
በርግጥ በእንዲህ አይነት ጅምላ ጨራሽ ጥቃት ውስጥ መምህርን መርጦ የሚተው ተአምር የለም፡ ይኽ ይጠፋቸዋል ብለን አንገምትም፡፡ ሆኖም ስለሔደው ከማሰብ በላይ ስለሚመጣው ማሰብ የባለተስፋዎች አለም መሆኑን ቢረዱ እንጂ፡፡ ግን ለምን መምህር? ታላላቅ ባለህልሞች እና ሳይንቲስቶች፣ ቀመር ፈጣሪች እና ተአምር ሰሪዎች ባሉባት ሀገር እኒህን ሰው መምህር እንደምን እራባቸው?
እንዲህ መስለኛል፤ ጃፓንን እዚህ ግቢ ከማትባልበት ሥፍራ አንስቶ ኃያል እና ታላቅ ያደረጋት እውቀት ፈላጊነት እንጂ እውቀት እራሱ አደለም፡፡ ይሔንን ደግሞ የሰጣት መምህራኗ ናቸው፡፡ እውቀት ለአንድ ውስን ነገር መፍትሔ ይሆናል፡፡ እውቀት ፈላጊነት ግን በማይቋረጥ ሂደት ውስጥ ችግሮችን እየፈቱ ምስጢሮችን ገሀድ እያወጡ መኖር ነው፡፡ በሌላ አባባል አንድ ኢንጂነር ህንጻ  ሰርቶ የመኖሪያ ችግርን ያቃልላል ለነዋሪው አኗኗሩን ግን ሊያሳየው አይቻለውም፡፡ አንድ ዶክተር በሽታን ያክማል እንጂ ጤናን አይጠብቅም፡፡ በፎቅ የመኖርን ስርአትም ሆነ ጤናውን ተከታትሎ የመጠበቅ ልማድ የእያንዳንዱ ሰው ፈንታ ነው፡፡ ደግሞም ሁለቱም የዛሬን ችግርን ቢያቃልሉ እንጂ ለነገው ችግር መፍትሔ አይሆኑም፡፡ ይሄን እውቀት ፈላጊነትን ሊሰጥ የሚችለው መምህር ብቻ ነው፤ መምህር ባለበት እውቀት መፈለግ ብርቱ ትሆናለች፡፡
እውቀትን መፈለግ ስትሰፋ ድንቁርና፣ ለኔ ይድላኝ ማለት እና ከኔ በላይ ማን አለብኝነት ስፍራ አይኖራቸውም፡፡ ህንጻዎችን በጥቂት ጊዜያት ውስጥ ሊገነቡና ከተማ በተንቆጠቆጡ የድንጋይ ጫካ ሊሞሉ ይችላሉ፡፡ እነዚህ ህንጻዎችን የኔ የሚላቸውና የእውቀት ፍሬ መሆናቸውን የሚረዳ የለማ ባለ አዕምሮ ህዝብ ከሌለን ግን እንደ ሔሮሽማ እና ናጋሳኪ ለመውደማቸው ከተሰሩበት ጊዜ እጅግ ያነሰ ሰአታት ብቻ ነው የሚወስደው፡፡
ዋናው ጭብጣችን እውቀትን መፈለግ ነው፡፡ ጃፓን ከዛ ሁሉ መአት ተርፋ አሁንም ታላቅ ሆና እንድትታይ ያደረጋት ምስጢር ይኽው እውቀትን ፍጊነቷ ነው፡፡ አንድ ህዝብ እውቀትን መፈለግ በመምህሩ ይማራል፡፡ ከትምህርት ቤት ከወጣ በኋላም ግን መምህሩ በሰጠው ዋና መሳሪያ አማካይነት እውቀትን ሲያስስ ይኖራል፡፡ ይህ መሳሪያ ደግሞ ንባብ ነው፡፡ ከንባብ ውጪ ሆነ ህዝብ ደካማ ነው፡፡  በተለይ በዚህ መረጃ ኃይል በሆነበት በዘመነ-ልዑላዊነት ውስጥ የማያነብ ህዝብ ያላት ሀገር የመጥፊያዋን ጉድጓድ እየቆፈረች ነው ማለት ይቀላል፡፡
እውቀትን የማያስስ ንባብን የሚጠላ ባለስልጣን የከበባት ሀገር መከራዋ ረዥም ነው፡፡ ዛሬ ያለንበትን ችግር ሁሉ መልስ ሚሰጡ በርካታ አቋራጮችን ልናገኝ እንችላለን፡፡ ድልድዮችን ህንጻዎችን እርሻዎችን መንዶችን የሚሰራ ድርጅት ከፍለን ከውጭ እናስመጣው ይሆናል፡፡ የተሰሩትን ስራዎች ምንገለገልባቸው ግን እኛው ነን፡፡ ደግሞም ለዛሬ ችግራችን መፍትሔ ሊሆኑ እንጂ ለነገው ችግራችን ዋስትና መሆን አይችሉም፡፡ ስለዚህም እውቀት አሳሽ፣ ንባብ ወዳድ ህዝብ ያስፈልገናል፡፡  
ይቀጥላል    

2013 ማርች 15, ዓርብ

የአያቴ ሐገር እንግዳ


ጊዜው ትንሽ ቆየት ብሏል፡፡ ለበርካታ ጊዜ አዲስ አበባ ሲመላለስ የማውቀው አያቴ እርጅና ተጭኖት ብቅ አልል ስላለ በዛውም ገጠሩን ማየት ስላማረኝ ሁለቱንም ልሳለማቸው ብዬ ጉዞ ጀመርኩ፡፡ ከዚህ ቀን አስቀድሞ ነፍስ ካወቅሁ በኃላ ማለቴ ነው እንዲህ ያለ ገጠር ውስጥ ገብቼ አላውቅም፡፡ በዛ ወቅት የመንግስት መገናኛ ብዙሀን እስከዛሬ የሐገሪቱን የጥቅም እፍታ ለብቻው ሲያግበሰብስ የነበረው ክልል ይህ እንደነበር ስለሚያወሩ የነበረኝ ምናባዊ ስዕል ትልቅ ነበር፡፡
አባይን ከተሸገርኩ በኋላ የማየው ትዕይን ግራ አጋባኝ፡፡ ያደፈ ጥብቆ ያደረጉ፣ ደሳሳ ጎጆዎቻቸው አካባቢ የከሱ የገረጡ ህጻናት እና ከብቶች የሞሉባቸው ጉስቁልናቸው እስከዛሬ ካየኋቸው ኢትዮጵያውያን የከፋ ህዝቦች ነበር የሚታዩኝ፡፡ የቆርቆሮ ቤት መኖር ለአካባቢው እንደስልጣኔ ተቆጥሮ ባለቆርቆሮ ቤቱ መንደር ይባላል ፡፡ በጉዞዬ ውስጥ በየማኃሉ የማገኛቸው ከተሞችን “ከተማ” ያልኳቸው ሌሎች ስላሏቸው ብቻ ነው፡፡ በዛ ላይ አንዱ ከአንዱ ያለው ርቀት ያስደነግጣል፡፡ በትንሹ ከአዲስ አበባ 200 ኪ.ሜ በማይሞላው ርቀት ላይ የምትገኘው አዋሳ እስክንደርስ ድረስ ስንት ትንንሽ ከተሞችን እንደምናይ ሳስበው ይህ ክልል አሳዘነኝ፡፡ 'ገጠሬነትን ክብር አድርጎ ራሱን ሲበላ የኖረ መሆኑን የሚነግረው አጥቷል ማለት ነው' ስል አሰብኩ፡፡ ባህርዳር ስደርስ ተስፋ ቆረጥኩ . . . ብዙም የሚጋነልላት አልሆነችልኝም፡፡ ያኔ በነበረው ህግ መሰረት አንድ የህዝብ ትራንስፖርት ወዲህ ሲመጣ ማደሪያውን የሚያደርገው የግድ ባህርዳር ላይ ነበር፤ ከመሸ መጓዝ አይፈቀድም፡፡
ከመኪና እንደወረድን ዳግመኛ ደብረታቦር የሚሄድ ሎንቺና ፈላልገን አገኘንና ከመሸ ገባን፡፡ በስም እና በዘፈን ብቻ አውቃቸው የነበሩትን አሞራ ገደል፣ ደንቢያ፣ ወረታን “በዚህ ነው” “ይሄ ነው” ባሉኝ ቁጥር እየተደነቅኩ እና እየተሸማቀቅኩ ነበር አጓጓዜ፡፡ ያኔ ነው “ለአፍ ዳገት የለውም” ብሂል የገባኝ፡፡ አሁን እነዚህ የደቀቁ እና የፈራረሱ ከተሞች ናቸው ለዘፈን በቅተው ድፍን አዲስ አበቤን ሲያምሱት የከረሙት? አልኩኝ ለራሴ፡፡ (በወቅቱ በርካታ የባህልና ዘመናዊ ሙዚቀኞች ጎጃምን እና ጎንደርን እየጠቀሱ ከከተማም አልፈው ጎጥና መንደሩን፣ ሳርና ቅጠሉን እያነሱ እንዲዘፍኑ የተገደዱ ይመስሉ ነበር) እንደውም ሳስበው ምናልባትም ለክልሉ እንዲህ ጠላት ያበበት ዘፈኖቹ ይመስሉኛል፡፡ ያልተመቸውን የሌለውን እያቆለጳጰ የዘረፈ አስመስለው ያቀረቡት ለማለት ከጅያለሁ፡፡


ደብረታቦር፡- አስገራሚ ነው! ከአንድ መቶ ሃምሳ አመታት በፊት በከተማነት የምትታወቅ ቢሆንም ዛሬ መንደርነት ትልቅ ክብር አለው፡፡ ድንጋጤዬ እየገዘፈ ነበር የሔደው፡፡ ሁለት ቀን ከገጠር ዘመዶች በቅሎ ይዘው እንዲመጡ መልዕክት ለመስደድ በገበያ ውስጥ ሰው ስናፈላልግ ቆየን. . . .፡፡ ሰው አግኝተን መልክታችንን ከነገርን በኋላ ግማሹን መንገድ ለማጋመስ ቀድመን ተነሳን፡፡ ካረፍንበት ሆቴል ልንወጣ ስናኮበኩብ አብረውኝ ከአዲስ አበባ የመጡት ሐገሩን ጠንቅቀው የሚያውቁት ወዳጆቼ የምንነግርህ ነገር አለ ብለው በስርአት እንዳዳምጣቸው ጠየቁኝ፡፡ 
“የሔውልህ ከዚህ በኋላ በምንም አይነት ማንም ሰው ስምህን ቢጠይቅህ እከሌ ነኝ አትበል፡፡ የማን ዘመድ ነህም ብትባል አትናገር” አሉኝ፡፡
ግራ ተጋባሁ. . . “ለምን?”
“ነገርንህ በቃ! ሲያነጋግሩህ እኛ መልስ እንሰጣለን፤ አንተ ቀድመህ መልስ አትስጥ ብቻ”
ምን እየተደረገ ነው ያለው? ግራ መጋባቴ ጨመረ . . . ከአዲስ አበባ አምኛቸው የመጣሁት እነሱን ነው፡፡ ሐገሩንም ጠንቅቀው ያውቁታል፡፡ የሩቅ ቢሆንም ዝምድና ሳይኖረን አይቀርም፡፡ ሆኖም ጊዜው አስተማማኝ አይደለም፡፡ ምንም የርስ በርሱ ጦርነት ከተጠናቀቀ ሰባት ዓመት ቢያልፈውም በየመንገዱ የተቃጠለ ታንክ እና የጦር መኪና ማየት ከብርቅ የሚቆጠር አይደለም፡፡ በዛ ላይ ሰዉ ሁሉንም በጥርጣሬ ሚያይ ስለሚመስል ባይተዋርነትን ያገዝፋል፡፡ ባጠቃላይ ሁኔታው ሁሉ ስጋቴን ሚጨምር እንጂ የሚያቃልል አይደለም፡፡
በዚህ አይነት ስሜት ውስጥ መቆየት አልፈለኩኝም፤ ጥያቄዬን አጠንክሬ ገፋሁበት፡፡
“ይኽውልህ የአካባቢው ሰው ማንን እንደሚጠላ እና ከማን ወዳጅነት እንዳለው አይታወቅም፡፡ አንተ ደግሞ ለሐገሩ እንግዳ ነህ፤ አይደለህም አንተ የትኛውንም ጸጉረ ልውጥን ደግሞ በቀላሉ ማወቅ ይችላሉ”
“እና?” ለጥያቄዬ በቀጥታ መልስ የሚሰጠኝ አላገኘሁም፡፡
“የአንተን አባት በቀላሉ ማንም ሰው የሚያውቀው ነው”
“ታዲያ ይሔ የምትሉኝ ጉዳይ ካባቴ ጋር የሚያገናኘው ምን ነገር አለ፡፡ ደግሞም አባቴ ከሞተ ሃያ ዓመት ሊሆነው ነው፡፡ ምንድን ነው ችግሩ?”
“አባትህ ጋ አይደለም ችግሩ የሚኖረው፡፡ አባትህ ከዚህ ሀገር ከወጣ ራሱ ሠላሳ ዓመት አልፎታል”
“የምትሉኝ አልገባኝም በግልጽ ያለውን ችግር ማወቅ ይኖርብኛል” አልኳቸው፡፡
“:ይሔውልኽ! ችግሩ አያትህ ጋር ነው”
“በግልጽ ንገሩኝ ምንድን ነው ችግሩ?”
ሁለቱም እርስ በርሳቸው ተያዩ. . .