ረቡዕ 13 ማርች 2013

እንዲህ ማሰቤን እንዲህ ላጽና


ው ሆኖ መፈጠር ለማሰብ ነው የሚሉ አሉና መስማማቴን ገልጬ ልንደርደር፡፡ መስማማቴ ግን ከራሴ ጋር ጠብ የሌለው /absolute/ ይደለም፡፡ የራሴን ሐሳብ አለመስማማቴ በራሱ ሁሌ አዲስ መሆኔን ያመለክትልኛልና እወደዋለሁ፡፡
አንዴ ጋሽ ስብሐት መድረክ ላይ ተቀምጦ በባዶ ሜዳ ጥርስ መንከስ ልማድ ከሆነባቸው ሰዎች መካከል አንዱ “በአንዱ መጽሐፍህ ላይ ሞትን የጭንቅ መሹለኪያ አድርገህ አክብረህ ትገልጸዋለህ. . . .ገጸ ባህሪህን በስሙኒ ገመድ ትሰቅላለህ፡፡ በሌላ አቅጣጫ ሞትን ረግመህ ከሞት የሚሸሹ ሰውን ታሞካሻለህ፡፡ ጋሽ ስብሀት በአንድ ጉዳይ ላይ ራሱ መስማማት ያቃተህ ይመስለኛል፡፡ አንተ ከየት ነህ?” ሲል ጠየቀው፡፡ የጋሽ ስብሐት መልስ አጭርና የማያሻማ ነበረች፡፡ “አሹ. . . .! (ደግ አደረግኩ እንደማለት) ድሮስ ቢሆን እኔ ስብሐት ‘ዳይናሚክ’ ነኝ፡፡ በትናንት ሐሳቤ ላይ ዛሬ ትፈልገኛለህ?” 
እውነቱን ነው ስብሐት፤ የሰው ልጅ ባለበት ቦታ የማይንቀሳቀስ ከነበረበት ሐሳቡ የማይለወጥ ከሆነ ሞቷል፣ አሊያም የእድገት ደረጃዎቹን አጉል ቦታ አቁሟል ማለት፡፡ ሰዎች የሰዎችን ሐሳብ እና እምነት ማክበር የሚችሉት በነሱ ውስጥ ያለውን ተቀያያሪነት /ዳናሚዝም/ን በቅጡ መረዳት ሲችሉ ነው፡፡ አሊያ በአለም ላይ አንድ እውነት እና እንድ እምነትን ለማሰልጠን ሲሉ አለምን ሲያተራምሱ ይኖራሉ፡፡ የፖለቲከኞቻችን ትልቁ ችግርም ይህ ነው፣ እነሱ ከቆሙበት አስተሳሰብ ውጪ ያለን ሁሉ ጠላት አድርገው መፈረጃቸው፡፡  
በወዳጅነት፣ በስራ አጋርነት፣ በጉርብትና ወይም በሌሎች ግንኙነታችን ውስጥ ያለንን አኗኗር የተረጋጋ እና መልክ ያለው ለማድረግ በእኛ ውስጥ ያለውን የሐሳብ እና የእምነት ተቀያያሪነትን መገንዘብ ጠቃሚው መንገድ ነው፡፡ በሌላ አባባል ዛሬ በሐሳቡ ያልተስማማን ሰው ነገ ሊለወጥና እኛ እውነት ነው ብለን ባሰብነው አቅጣጫ ሊቆም የሚችል መሆኑን በማመን እድልና ጊዜ ልንሰጠው ይገባል፡፡ እናም እንዲህ ማሰቤን ለማጽናት የኔን ተለዋጭነትንም በማመን ላይ መሆን ይኖርበታል፡፡ ይሄንን ሐሳቤን ደግሞ ነገ ልንደው እችል ይሆናልና፡፡
እረ ሲጀምርም እንዲህ ብዬ ለመጻፍ አልተነሳሁም ነበር፡፡ እንዲህ ሆኖ አለቀ እንጂ፡፡
27/6/2005


  


ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ